ከጠቀማችሁ!
፩) ለአንድ ሰው ከሁለቴ በላይ አይደውሉ። ካላነሱ ምናልባት ወይ አላዩትም፣ ወይ ለማንሳት የሚመች ቦታ አይደሉም፣ ወይ ደግሞ ማንሳት አልፈለጉም። ስለዚህ መልሰው እስኪደውልሎዎት ይጠብቁ።
፪) የተበደራችሁትን ገንዘብ አበዳሪው ከማስታወሱ ወይም ከመጠየቁ በፊት ይመልሱ። ይሄ የታማኝነታችሁ ወይም የመልካም ስብዕናችሁ መገለጫ ነው። ምልሰቱ ከእስክሪብቶ፣ ከእስርሳስ ሊጀምር ይችላል።
፫) አንድ ሰው ሆቴል ሲጋብዛችሁ ውድ ምግቦችን እና መጠጦችን ከማዘዝ ይቆጠቡ። ምክንያቱም ያስገምታችኋል።
፬) "እስካሁን ለምን አላገባህ/ሽም፤ ልጆች ለምን አልወለድክ/ሽም፤ አይነት በጣም ደባሪ ጥያቄዎችን አትጠይቁ። በፈጣሪ ስም! ይሄ የእናንተ ችግር አይደለም።
፭) ከኋላችሁ የሚመጣ ሰው ካለ በሩን ከፍታችሁ የማስገባት ልምድ ይኑራችሁ። ሴት ትሁን ወንድ፤ ታላቅ ይሁን ታናሽ ማተር አያደርግም። ሰዎችን በማክበር እናንተ አትዋረዱም።
፮) ጓደኛችሁ ዛሬ የታክሲ ከከፈለ፣ ነገ እናንተ ለመክፈል ሞክሩ።
፯) ልዩነቶችን ያክብሩ። ለእናንተ 6 ቁጥር የመሰለው ለሌላው 9 ቁጥር ሊመስል ይችላልና ሐሳቡን እንደተቀናቃኝ ሳይሆን እንደአማራጭ ለመውሰድ ይሞክሩ።
፰) የሰዎችን ንግግር አያቋርጡ። እስኪጨርሱ በሚገባ አድምጠው የእርሶን ሐሳብ ይቀጥሉ።
፱) ሰው ላይ አፊዘው ደስተኛ መስለው ካልታዩ በድጋሚ እንዳትቀልዱባቸው። ምክንያቱም የእርሶ ሽንቁር ሌላውን ለማስገብት በር ትሆናለች።
፲) በማንኛውም ነገር እርዳታ ስታገኙ "አመሰግናለሁ" ማለትን ልመዱ።
፲፩) ሰውን በሕዝብ ፊት ያወድሱ፣ ለብቻ ይገስፁ።
፲፪) የሰው መልክ፣ ቁመና፣ ፀባይ፣ ውፍረት… ላይ ምንም አስተያየት የመስጠት በቂ ምክንያት የላችሁም። ማለት ያለባችሁ ነገር ቢኖር "ውብ ናችሁ" ብቻ ነው። የምትናገሩት ቃል መልካም ካልሆነ ግን ዝምታን ይልመዱ።
፲፫) ሰዎች አንድ ፎቶ ብቻ ለማሳየት ፈልገው ስልካቸውን ሲሰጧችሁ ወደፊት፣ ወደኋላ አያድርጉ። ምክንያቱም ቀጣዩ ምን እንደሆነ አታውቁም።
፲፬) ጓደኛችሁ የሕክምና ቀጠሮ እንዳላቸው ከነገሯችሁ ምን እንደሆነ በፍፁም እንዳትጠይቋቸው። "እንደሚሻልህ/ሽ ተስፋ አደርጋለው" ብቻ ይበሉ። የጤና እክላቸውን ተናግረው የሚረብሽ ኹኔታ ውስጥ እንዳትከቷቸው ተጠንቀቁ። እነሱ መንገር ከፈለጉ ያለናንተ ጥያቄ ይነግሯችኋል።
፲፭) ለዶክተር፣ ለባለስልጣን፣ ለባለፀጋ ክብር በምትሰጡት ልክ ለፅዳት ሰራተኛም፣ ለተራው ዜጋም፣ ለነዳዲያንም ስጡ። ሰውን መናቅ ብልግናችሁን ቢሆን እንጂ ሌላ ምንም አያሳይም። ሁሉንም ሰው በእኩል አይን ማክብር ትልቅነት ነው።
፲፮) ሰዎች ፊት ለፊት እየተመለከቱ ሲያናግሯችሁ ሞባይል፣ ኮምፒተር ወይም መጻሕፍትም ላይም ቢሆን ተተክላችሁ አትመልሱ። ተገቢ አይደለም። በወቅቱ ቀዳሚው መሆን የሚገባው ሰዎቹ እንጂ ቁስ አይደለም።
፲፯) ከረጅም ጊዜ በኋላ ጓደኛችሁን ወይም ወዳጃችሁን ካገኟችኋቸው እነሱ ለመናገር ካልፈቀዱ በስተቀር ስለኑሯቸው፣ ስለሕይወታቸው ከመጠየቅ ተቆጠቡ።
፲፰) በቀጥታ የሚመለከታችሁ ነገር ከሌለ በስተቀር በማያገባችሁ ጉዳይ አትግቡ።
፲፱) ሰዎች እመንገድ ሲያናግሯችሁ የአክብሮት ምልክት በመሆኑ የፀሐይ መነፅራችሁን የማውለቅ ልምድ ይኑራችሁ። ከቃላት እኩል የአይን ግንኙነት ጠቃሚ ነው።
፳) ስለባለፀግነታችሁ በነዳዲያን ፊት ከመለፍለፍ ይቆጠቡ። በተመሳሳይ ስለልጆች በመሃኖች ፊት አያንሱ።
፳፩) ካልተጠየቃችሁ በስተቀር ለማንም ምክር ለመስጠት እትሞክሩ። "ባንተው ምክር ሄጄ፣ ባንተው አስጨከንከኝ" እንዳለው ድምፃዊ አንተስ ምን እያደረክ ነው ካላችሁኝ ምናልባት ይሄ በጥቆማ ደረጃ ከተወሰደ ቢሆን እንጂ ምክር መሆን የሚችል ስላልመሰለኝ ነው። ምክር ነው ብላችሁ ካሰባችሁ ግን ሁሉንም ዝለሉት።
ቸር ጊዜ!
ታላቁን ህዝብ የማይመጥን ታላቅ ችግር ተጋብቶናልና ታግለን እናስወግደው።
ከአባትና እናቶቻችን የወረስነው አንድነትን፣ ፍቅርን እና መቻቻልን አለፍ ሲልም የሀገርና የህዝብ ጠላትን በጋራ ቆሞ መታገል እንጂ ወንድምን መግደል እና በሰው ደም መስከርን አይደለም!!!
ህዝባችን መልካም እሴቶች እና ውብ ባህሎች ማለትም፥ ፍቅር፣ መተሳሰብ፣ አብሮ መኖር፣ አንድነት፣ መደጋገፍ እና ሌሎችንም ውብ መገለጫዎች አቅፎ የመጣና እየኖረ ያለ ታላቅ ህዝብ ነው። ህዝባችን በመልካም ባህል የተገነባ እና ፈጣሪውን አብዝቶ የሚፈራ ህዝብ ሆኖ ሳለ አሁን የኔ ዘመን ትውልድ ለምን እርስ በርሱ ይገዳደላል? ምን አይነት ክፉ ልማድ ነው እየተለማመድን ያለነው?
በትውልዱ ዘንድ አሁን አሁን እየታየ ያለው አደገኛ ነገር፥ እራስ ወዳድነት፣ ስግብግብነት፣ በህሊና ቢስነት፣ ስሜታዊነት፣ ግብታዊነት እና ጨካኝነት ነው።
ካለ ምንም ርህራሄ የፈጣሪን ህንፃ የማፍረስ ልክፍት እየበዛ መጥቷል። ወንድም የወንድሙን ደም በጭካኔ ለማፍሰስ ይጣደፋል።
በጣም የሚያሳዝነው ደግሞ ሰውን የገደለን ሰው ከመርገምና ከማውገዝ ይልቅ ነፍሰ ገዳይን ሲያሞግስ የሚውል ሰው መታዬቱ ነው።
ይህ ልምምድ አደገኛ እና መጥፎ ልምምድ ነው። የአባቶቻችንም አይደለም። በተለይ የዚህን ዘመን ሰዎች አይመጥነንም። ይህ አደገኛ ልምምድ በጣም እየጎዳን ነው። ወደ ኋላ እየመለሰን እና ከፈጣሪም ጋር እያጣላን ነው። ስለሆነም አምርረን ልንታገለው ይገባል። ከግል ፍላጎትና ስሜት እንዲሁም ከእራስ ወዳድነት ስሜት ወጥተን በቻልነው አቅም ስለ አንድነት እና ስለ ፍቅር እናስብ። ችግሮች ቢኖሩ እንኳን በመወያየት እና በመደማመጥ እንፍታ። ቢያንስ ዘመኑን የሚመጥን ዕሳቤ እንላበስ። ፈጣሪያችንንም እንፍራ።
ፈጣሪ ፍቅርና ሰላምን፤ ማስተዋልና ጥበብን ይስጠን! ከክፋት እና ከተንኮል ያርቀን!